Jeremiah 23

ጻድቁ ቅርንጫፍ

1“በማሰማሪያ ቦታዬ ያሉትን በጎቼን ለሚያጠፉና ለሚበትኑ እረኞች ወዮላቸው!” ይላል እግዚአብሔር 2ስለዚህ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሕዝቤን ስለሚጠብቁ እረኞች እንዲህ ይላል፤ “መንጋዬን ስለ በተናችሁ፣ ስላባረራችሁና ተገቢውን ጥንቃቄ ስላላደረጋችሁላቸው፣ ለክፋታችሁ ተገቢውን ቅጣት አመጣባችኋለሁ” ይላል እግዚአብሔር 3“የመንጋዬንም ቅሬታ ካባረርሁባቸው አገሮች ሁሉ እኔ ራሴ ሰብስቤ፣ ወደ መሰማሪያቸው እመልሳቸዋለሁ፤ በዚያም ፍሬያማ ይሆናሉ፤ ይበዛሉም። 4የሚጠብቋቸውን እረኞች አስነሣላቸዋለሁ፤ ከእንግዲህም አይፈሩም፤ አይደነግጡም፤ ከእነርሱም አንድ እንኳ አይጐድልም” ይላል እግዚአብሔር

5“እነሆ፤ ለዳዊት፣
ወይም ከዳዊት የዘር ግንድ

ጻድቅ ቅርንጫፍ የማስነሣበት ጊዜ ይመጣል፤
እርሱም ፍትሕንና ጽድቅን የሚያደርግ፣
በጥበብ የሚገዛ ንጉሥ ይሆናል” ይላል እግዚአብሔር
6በእርሱም ዘመን ይሁዳ ይድናል፤
እስራኤልም በሰላም ይኖራል፤
የሚጠራበትም ስም፣
እግዚአብሔር ጽድቃችን”
የሚል ነው።
7“ስለዚህ ሰዎች፣ ‘እስራኤላውያንን ከግብፅ ምድር ያወጣ ሕያው እግዚአብሔርን!’ ብለው ከእንግዲህ የማይምሉበት ዘመን ይመጣል ይላል እግዚአብሔር 8ነገር ግን፣ ‘እስራኤልን ከሰሜን ምድርና እነርሱን ከበተነባቸው ከሌሎች አገሮች ያወጣ ሕያው እግዚአብሔርን’ ይላሉ፤ ከዚያ በኋላ በገዛ ምድራቸው ይኖራሉ።”

ሐሰተኛ ነቢያት

9ስለ ነቢያት፣

ልቤ በውስጤ ተሰብሯል፤
ዐጥንቶቼም ተብረክርከዋል፤
ከእግዚአብሔር የተነሣ፣
ከቅዱስ ቃሉም የተነሣ፣
የወይን ጠጅ እንዳሸነፈው፣
እንደ ሰካራም ሰው ሆኛለሁ።
10ምድሪቱ በአመንዝሮች ተሞልታለች፤
ከርግማን የተነሣ
ወይም ከእነዚህ ነገሮች የተነሣ
ምድሪቱ ታለቅሳለች፤
በምድረ በዳ ያሉት መሰማሪያዎች ደርቀዋል።
ወይም ምድሪቱ ደርቃለች

ነቢያቱም ጠማማ መንገድ ተከትለዋል፤
ሥልጣናቸውን ያለ አግባብ ተጠቅመዋል።

11“ነቢዩም፣ ካህኑም በጽድቅ መንገድ የማይሄዱ ናቸው፤
በቤተ መቅደሴ እንኳ ሳይቀር ክፋታቸውን አይቻለሁ።”
ይላል እግዚአብሔር
12“ስለዚህ መንገዳቸው ድጥ ይሆናል፤
ወደ ጨለማ ይጣላሉ፤
ተፍገምግመውም ይወድቃሉ፤
በሚቀጡበትም ዓመት፣
መዓት አመጣባቸዋለሁ፤”
ይላል እግዚአብሔር
13“በሰማርያ ባሉ ነቢያት ላይ፣
ደስ የማያሰኝ ነገር አይቻለሁ፤
በበኣል ስም ትንቢት ተናገሩ፤
ሕዝቤን እስራኤልን አሳቱ።
14በኢየሩሳሌም ባሉ ነቢያትም ላይ፣
የሚዘገንን ነገር አይቻለሁ፤
ያመነዝራሉ፤ በመዋሸትም ይኖራሉ፤
ማንም ከክፋቱ እንዳይመለስ፣
የክፉዎችን እጅ ያበረታሉ፤
በእኔ ዘንድ ሁሉም እንደ ሰዶም፣
ነዋሪዎቿም እንደ ገሞራ ናቸው።”
15ስለዚህ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ስለ እነዚህ ነቢያት እንዲህ ይላል፤

“ከኢየሩሳሌም ነቢያት፣
በምድሪቱ ሁሉ ርኩሰት ተሠራጭቷልና፤
መራራ ምግብ አበላቸዋለሁ፤
የተመረዘም ውሃ አጠጣቸዋለሁ።”
16የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤

“እነዚህ ነቢያት የሚተነብዩላችሁን አትስሙ፤
በባዶ ተስፋ ይሞሏችኋል፤
ከእግዚአብሔር አፍ የወጣ ሳይሆን፣
ከገዛ ልባቸው የሆነውን ራእይ ይናገራሉ።
17እኔን ለሚንቁኝ፣
እግዚአብሔር ሰላም ይሆንላችኋል ብሏል’ ይላሉ፤
የልባቸውን እልኸኝነት ለሚከተሉም ሁሉ፣
‘ክፉ ነገር አይነካችሁም’ ይሏቸዋል።
18ቃሉን ለማየትና ለመስማት፣
እነማን የእግዚአብሔር ምክር ባለበት ቆመዋል?
ቃሉን ያደመጠ፣ የሰማስ ማን ነው?
19እነሆ፤ የእግዚአብሔር ዐውሎ ነፋስ፣
በቍጣ ይነሣል፤
ብርቱም ማዕበል፣
የክፉዎችን ራስ ይመታል።
20 እግዚአብሔር የልቡን ሐሳብ፣
ሙሉ በሙሉ ሳይፈጽም፣
ቍጣው እንዲሁ አይመለስም፤
በኋለኛው ዘመን፣
ይህን በግልጽ ትረዳላችሁ።
21እኔ እነዚህን ነቢያት አልላክኋቸውም፤
እነርሱ ግን ለራሳቸው መልእክታቸውን ይዘው ሮጡ፣
ሳልናገራቸውም፣
ትንቢት ተናገሩ።
22ምክሬ ባለበት ቢቆሙ ኖሮ፣
ቃሌን ለሕዝቤ ባሰሙ ነበር፤
ከክፉ መንገዳቸው፣
ከክፉ ሥራቸውም በመለሷቸው ነበር።

23“እኔ የቅርብ አምላክ ብቻ ነኝን?”
ይላል እግዚአብሔር
“የሩቅስ አምላክ አይደለሁምን?
24እኔ እንዳላየው፣
በስውር ቦታ ሊሸሸግ የሚችል አለን?”
ይላል እግዚአብሔር
“ሰማይንና ምድርንስ የሞላሁ እኔ አይደለሁምን”
ይላል እግዚአብሔር
25“ ‘ሕልም ዐለምሁ ሕልም ዐለምሁ’ እያሉ በስሜ የሐሰት ትንቢት የሚናገሩትን የነቢያትን ቃል ሰምቻለሁ፤ 26ይህ ነገር፣ የገዛ ልባቸውን ሽንገላ በሚተነብዩ በሐሰተኞች ነቢያት ልብ ውስጥ የሚቈየው እስከ መቼ ነው? 27አባቶቻቸው በኣልን በማምለክ ስሜን እንደ ረሱ፣ እነርሱ በሚነጋገሩት ሕልም፣ ሕዝቤ ስሜን እንዲረሳ ያደረጉ ይመስላቸዋል። 28ሕልመኛ ነቢይ ሕልሙን ያውራ፤ ቃሌ ያለው ግን በታማኝነት ይናገር፤ ገለባና እህል ምን አንድ አድርጓቸው!” ይላል እግዚአብሔር 29“ቃሌ እንደ እሳት፣ ድንጋይንም እንደሚያደቅቅ መዶሻ አይደለምን?” ይላል እግዚአብሔር

30“ስለዚህ ቃሌን እርስ በእርስ በመሰራረቅ ከእኔ እንደ ተቀበሉ አድርገው የሚናገሩትን ነቢያት እቃወማለሁ” ይላል እግዚአብሔር 31“አፈጮሌነታቸውን በመጠቀም፣ ‘እግዚአብሔር እንዲህ ይላል’ የሚሉትን ነቢያት እቃወማለሁ” ይላል እግዚአብሔር 32“እነሆ፤ ሐሰተኛ ሕልም ተመርኵዘው ትንቢት የሚናገሩትን ነቢያት እቃወማለሁ” ይላል እግዚአብሔር፤ “እኔ ሳልልካቸው ወይም ሳልሾማቸው ደፍረው ውሸት ይናገራሉ፤ ሕዝቤንም ያስታሉ፤ ለዚህም ሕዝብ አንዳች አይረቡትም” ይላል እግዚአብሔር

የእግዚአብሔር ሸክም ምንድን ነው?

33“ይህ ሕዝብ ወይም ነቢይ ወይም ካህን፣ ‘የእግዚአብሔር ሸክም ምንድን ነው?’ ብለው ቢጠይቁ፣ ‘ሸክሙ እናንተ ናችሁ፤
ወይም ንግር። (ለንግር እና ለሸክም የሚተካው የዕብራይስጥ ቃል አንድ ዐይነት ነው።)
እወረውራችኋለሁ’ ይላል እግዚአብሔር ብለህ መልስላቸው።
34ነቢይ ወይም ካህን ወይም ማንኛውም ሰው፣ ‘የእግዚአብሔር ሸክም’ እያለ ቢናገር፣ ያን ሰውና ቤቱን እቀጣለሁ። 35እያንዳንዱ ለባልንጀራው ወይም ለዘመዱ፣ ‘እግዚአብሔር ምን መልስ ሰጠ?’ ወይም፣ ‘እግዚአብሔር ምን ተናገረ?’ ማለት ይገባዋል። 36ከእንግዲህ ግን፣ ‘የእግዚአብሔር ሸክም’ ብላችሁ መናገር አይገባችሁም፤ ምክንያቱም ለሰው ሁሉ የገዛ ራሱ ቃል ሸክሙ ስለሚሆን፣ የአምላካችንን የሰራዊት ጌታ የእግዚአብሔርን፣ የሕያው አምላክን ቃል ታጣምማላችሁ። 37ስለዚህ ለነቢዩ፣ ‘እግዚአብሔር ምን መልስ ሰጠህ?’ ወይም፣ ‘እግዚአብሔር ምን ተናገረህ?’ ትለዋለህ፤ 38የእግዚአብሔር ሸክም’ ብትሉ እንኳ፣ እግዚአብሔር ግን እንዲህ ይላል፤ ‘እኔ፣ “የእግዚአብሔር ሸክም” አትበሉ’ ብዬ ብነግራችሁም፣ እናንተ፣ ‘የእግዚአብሔር ሸክም’ ብላችኋል፤ 39ስለዚህ እናንተን፣ እንዲሁም ለእናንተና ለአባቶቻችሁ የሰጠኋትን ከተማ ጭምር ፈጽሜ እተዋችኋለሁ፤ ከፊቴ እጥላችኋለሁ፤ 40ለዘላለም የማይረሳ ዕፍረት፣ የዘላለምም ውርደት አመጣባችኋለሁ።”

Copyright information for AmhNASV